ዜናዎች | 02.09.2010 | 15:00 UTC
ዋሽንግተን-የእስራኤል-ፍልስጤም ቀጥታ ድርድር
የእስራኤል ጠቅላይ ሚንስትር ቤንያሚን ኔታንያሁና የፍልስጤም ራስ ገዝ ፕሬዝዳት ማሕሙድ አባስ ዛሬ ዋሽንግተን ዉስጥ የፊት ለፊት ድርድር ጀመሩ።ድርድሩ እንዲጀመር ከፍተኛ ግፊት ያደረጉት የዩናይትድ ስቴትሱ ፕሬዝዳት ባራክ ኦባማ ትናንት የግብፁ ፕሬዝዳት ሆስኒ ሙባረክና የዮርዳኖሱ ንጉስ አብደላሕ በተገኙበት ሁለቱን መሪዎች ራት ጋብዘዋቸዉ ነበር።ኦባማ ሁለቱን መሪዎች በተናጥል ካነጋገሩ በሕዋላ እንዳሉት «ለሰላም ጥሩ እድል» ያሉትን አጋጣሚ መሪዎቹ ሊጠቀሙበት ይገባል።
«ይሕን መሰሉ ጥሩ አጋጣሚ ምናልባት በቅርቡ ተመልሶ እንደማይመጣ ለእያንዳዳቸዉ ነግሬያቸዋለሁ። እንዲያመልጣቸዉ ሊፈቅዱ አይገባም።ሕዝቦቻቸዉ ሊያገኙት የሚገባቸዉን ሠላም ለማዉረድ የመሪዎች ብራታትና ራዕይ የሚፈተንበት ጊዜ አሁን ነዉ።አመሰግናለሁ።»
ድርድሩ ከዚሕ ቀደም እንደተደረጉት ሁሉ በበርካታ ልዩነቶችና እንቅፋቶች የተሞላ ነዉ።ይሁንና በዩናይትድ ስቴትስ ዋና ሸምጋይነት የሚደረገዉ ድርድር ባንድ አመት ጊዜ ለዉጤት ይበቃል የሚል እቅድ ተይዞለታል።ሁለቱ መሪዎችም ሠላም ለማዉረድ እንደሚጥሩ አስታዉቀዋል።የእስራኤሉ ጠቅላይ ሚንስትር ለሰላም የሚገባዉን ዋጋ ለመክፈል ነዉ-የመጣሁት ብለዋል።«ዛሬ እዚሕ የመጣሁት፥ ሕዝቦቻችን በሠላም፥ በደሕንነትና በክብር እንዲኖሩ ታሪካዊ ማካካሻ ለማድረግ ነዉ።»
የፍልስጤሙ ፕሬዝዳት በበኩላቸዉ እንዳሉት በሁሉም ችግሮች ላይ ለመደራደር ዝግጁ ናቸዉ።
«ጠንክረን መስራት አለብን።በድርድሩ ሒደት ሁሉንም ችግሮች አንስተን መነጋገር አለብን።ሥለ እየሩሳሌም፥ሥለ ሥደተኞች፥ሥለ ሠፈራ መንደሮች፥ ሥለ ድንበር፥ ሥለ ዉሐ እጥረት፥ እስረኞቻችን በሙሉ ሥለሚፈቱበት ሁኔታ ሁሉ መነጋገር አለብን።»
የእስራኤልና የፍልስጤም መሪዎች ፊት ለፊት ተገናኝተዉ ሲደራደሩ በሃያ-ወራት ዉስጥ ያሁኑ የመጀመሪያቸዉ ነዉ።የኔትንያሁ መንግሥት የአይሁድ ሠፈራ መንደሮች ግንባታን ሙሉ በሙሉ አለማቆሙ፥የፍልስጤም ታጣቂዎች ባለፈዉ ማክሰኞ አራት አይሁድ ሠፋሪዎችን መግደላቸዉ እና አክራሪዉ ደፈጣ ተዋጊ ቡድን ሐማስ እስራኤልን ማጥቃቱን እንደሚቀጥል መዛቱ የድርድሩን ተስፋ እንዳጨናጉሉት እያሰጋ ነዉ።









